የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት ታሪክ እና አደረጃጀት
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በዳግማዊ አፄ ምኒልክ ዘመነ መንግስት በ1879 ዓ.ም የተቆረቆረች ሲሆን 139 ዓመት ዕድሜዋ ላይ ትገኛለች፡፡ ከተማዋ ከተመሠረተችበት ጊዜ ጀምሮ የተለያዩ የአስተዳደር ዘይቤዎችንና ስርዓቶችን ስታስተናግድ የቆየች ሲሆን በነዋሪዎቿ የነቃ ተሳትፎ ለከተማዋ እድገትና ለሀገር ግንባታ የበኩሏን ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ አስተዋፅኦ ያበረከተችና አሁንም በማበርከት ላይ የምትገኝ ናት፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት የከተማው ህግ አውጪ ተቋም ሲሆን በከተማ አስተዳደሩ ላይ የሚደረጉ ውሳኔዎችን በማሻሻልና በማረጋገጥ ረገድ ዋና ሚና ይጫወታል።
የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት በኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ ህገ መንግሥት አንቀጽ 49፣ በአዋጅ ቁጥር 361/1995 ተሻሽሎ በወጣው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ማቋቋሚያ ቻርተር መሠረት ግንቦት 12 ቀን 2000 ዓ.ም ትክክለኛውን የምክር ቤት ቅርፅ የያዘ የመጀመሪያው የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት ተመሰረተ፡፡
ምክር ቤቱ እንደ ህዝብ እንደራሴነት ራሱን ችሎ ሲቋቋም የመጀመሪያው ሲሆን ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ማለትም ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ የተጣለበትን ኃላፊነት ለመወጣት ከተማ አቀፍ ህጐችን በማውጣት ለከተማዋ ነዋሪ ተደራሽ ከማድረግ ጐን ለጐን በከተማው የሚገኙ አስፈፃሚ አካላት ከተቋቋሙበት ዓላማና ተልዕኮ አንፃር ለህብረተሰቡ የተቀላጠፈ አገልግሎት በመስጠት ላይ መሆናቸውን በቋሚ ኮሚቴዎች በኩል እየተከታተለ ድጋፎችንም ሲሰጥ የቆየና አሁንም የዘወትር ተግባሩን ያለመታተር በማከናወን ላይ የሚገኝ የህዝብ ምክር ቤት ነው፡፡