የተከበሩ ወ/ሪት ፈይዛ መሐመድ ዑመር

የአዲስ አበባ ምክር ቤት ምክትል አፈ-ጉባኤ

የአዲስ አበባ ከተማ ም/ቤት በተሻሻለው የከተማ አስተዳደሩ ቻርተር አዋጅ ቁጥር 361/1995 መሰረት በይፋ ምስረታውን ካደረገ በኋላ በሶስት የምርጫ ዘመን በመራጩ ህዝብ የተሰጠውን ይሁንታ አግኝቶ የህዝብ እንደራሴነቱን በውል ለመወጣት በርካታ ተግባራትን እየከወነ ይገኛል፡፡
ምክር ቤቱ ለከተማ አስተዳደሩ የሚወጡ ህጎች የነዋሪውን ማህበራዊ ፖለቲካዊ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን የሚያረጋግጡ መሆናቸውን እያረጋገጠ ህግ ከማውጣት ባሻገር አስፈፃሚው አካል የወጡ ህጎች በአግባቡ መተግበራቸውንና ተቋማት ለህብረተሰቡ የሚሰጡት አገልግሎት በህብረተሰቡ አዳጊ የአገልግሎት ፍላጎት ልክና ዘላቂ ልማትን መሰረት ያደረጉ መሆናቸውን በክትትልና ቁጥጥር እያረጋገጠ ችግር ባለባቸው ስራዎች ደግሞ የአፈፃፀም አቅጣጫ እየሰጠ ለህብረተሰቡ ዘላቂ የልማት ጥያቄ ምላሽ ለማስጠት አበክሮ ይሰራል፡፡
የምክር ቤት አባላቱን የልማት ተሳትፎ በማሳደግ ረገድ ከመረጣቸው ህዝብ ጋር ቀጥታ ተሳትፎ እንዲኖራቸው በመራጭ ተመራጭ የትስስር አደረጃጀት መድረክ የነዋሪውን የልብ ትርታ በማድመጥ መራጩ ህዝብ በጥብቅ የሚፈልገውን የመልካም አስተዳደርና ቀልጣፋ የአገልግሎት አሰጣጥ እንዲያገኝ ለማስቻል የምክር ቤት አባላቱ አይነተኛ የህዝብ እንደ ራሴነታቸውን በዚሁ የመራጭ ተመራጭ አደረጃጀት መድረክ ሚናቸውን እየተወጡ ይገኛል፡፡
በመሆኑም እነዚህንና ሌሎች ምክር ቤቱ በሚያከናውናቸው ዘርፈ ብዙ የስራ እንቅስቃሴዎች የህብረተሰቡን ጥቅም ለማረጋገጥ በምናደርገው ጥረት ሁሉም የከተማችን ነዋሪዎች የበኩላችሁን ሚና እንድተወጡ እያሳሰብኩ ለከተማችን ብሎም ለሀገራችን እድገት በአብሮነት በጋራ እንድንሰራ ጥሪዬን አስተላልፋለሁ፡፡

አመሰግናለሁ!